Description
ክርስትና
ስም አንድ ሰው ከሌላው ተለይቶ የሚታወቅበት ነው። ሰው ከእናትና ከአባቱ ሲወለድ ስም እንደሚወጣለት ሁሉ በጥምቀት ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ሲወለድም ስም ይወጣለታል፡፡ ስለዚህ አንድ ክርስቲያን ሁለት ዓይነት ስሞች ሊኖሩት ይችላል። አባትና እናት የሚያወጡለት ስም የተጸውኦ ስም ይባላል፡፡ በጥምቀት ጊዜ የሚወጣለት ስም ደግሞ የክርስትና ስም ይባላል፡፡ በጥምቀት ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ይገኝበታል፡፡ በክርስቶስ የሚያምን ሰው ክርስቲያን ሲባል እምነቱ ደግሞ ክርስትና ይባላል። ክርስቲያን ማለት የክርስቶስ ወገን የሆነ ማለት ነው። በመሆኑም በክርስቶስ አምነን በሥላሴ ስም መጠመቃችንን የሚገልጸው ስም ስመ ክርስትና ይባላል። ስያሜውም ተጠማቂው ከተጠመቀበት ዕለት ጋር ተያይዞ ሊሰየም ይችላል። በመንፈሳዊ አገልግሎት ስንሳተፍ ስመ ክርስትናችንን እንጠቀማለን፡፡ የክርስትና ስም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትውፊት ያለው ነው፡፡ ይህም እግዚአብሔር አብራምን አብርሃም፣ ያዕቆብን እስራኤል፣ ሰምዖንን ጴጥሮስ፣ ሳውልን ጳውሎስ እንዲባል እንዳደረገው ያለ ነው፡፡
የክርስትና ስም አንድ የሚጠመቅ ሰው በሚያጠምቀው ካህን የሚሰጠው ወይም የሚጸድቅለት ስያሜ ነው፡፡በቤተ ክርስትያናችን ለመጀመሪያ ጊዜ ስመ ክርስትና ያወጣ አባት የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጳጳስ ታላቁ ኣባት አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ሲሆን ስመ ክርስትና የወጣላቸው ደግሞ ኢዛናና ሳይዛና ናቸው።ኢዛናን አብርሃ ሳይዛናን አፅብሃ ብለው ሰይመዋቸዋል።
ይህንን ስም ቤተክርስቲያን ዝም ብላ ለህጻናቱ የምትለጥፍ የሚመስላቸው ሰዎች ቀላል አይደሉም፡፡በጥምቀት ጊዜ ቤተክርስቲያን ልጆቿን ስትቀበል እንዲሁ አይደለም ተገቢ ስም አውጥታ ከመንፈስ ቅዱስ በጥምቀት ዳግመኛ ወልዳ ቅበዐ ሜሮን ቀብታ የሚንከባከብ የክርስትና አባት እናት ሰይማ በመስቀሉ ቃል አስገብታ ቅዱስ ስጋና ደሙን መግባ ነው፡፡
ስለዚህ ስርአቱን በመጠቀም ከሚገኘው በረከት ተሳታፊዎች እንድንሆን አምላክ ይርዳን፡፡
በጥምቀት ከማይጠፋ ዘር የወለደን፣ በሞቱና በትንሣኤው እንመስለው ዘንድ ተጠምቆ ተጠመቁ ያለን የቅዱሳን አምላክ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀት የተሰጠንን የልጅነት ጸጋ ይጠብቅልን፤ ለዚህ ጸጋ ያልበቁትን ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግቢያ ያመጣልን ዘንድ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን፡፡