Description
ሙሉ ፍትኅት
ፍትሐት ማለት ከዚህ ዓለም በሞት ለሚለዩ ሰዎች በሕይወተ ሥጋ ሳሉ ከሠሩትና ከፈጸሙት በደል እንዲነጹ ከማእሠረ ኃጢአት እንዲፈቱ ወደ እግዚአብሔር የሚቀብ ጸሎት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሙታን ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግ ታዝዛለች፡፡
ጸሎተ ፍትሐት ለበደሉት ሥርየት ኃጢአትን፣ ይቅርታን ዕረፍተ ነፍስን ያሰጣል፡፡ ለደጋጎች ደግሞ ክብርን፣ ተድላን፣ ዕረፍትን ያስገኛል፡፡
ሙታንና ሕያዋን የሚገናኙት በጸሎት አማካኝነት ነው፡፡ ሕያዋን ለሙታን ይጸልያሉ፤ ሙታንም ለሕያዋን ይለምናሉ፡፡ /ሄኖ. 12፤34/ ሕያዋን ለሙታን የሚጸልዩት ጸሎትና የሚያቀርቡት መሥዋዕት በግልጽ እንደሚታይ ሁሉ ሙታንም በአጸደ ነፍስ ሆነው በዚህ ዓለም ለሚቆዩ ወገኖቻቸው ሕይወትና ድኅነትን፣ ስርየተ ኃጢአትንና ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን፣ ጽንዓ ሃይማኖትን እንዲሰጣቸው፣ በንስሐ ሳይመለሱ፣ ከብልየተ ኃጢአት ሳይታደሱ እንዳይሞቱ ፈጣሪያቸውን ይለምናሉ፡፡ ይህም ሥርዓት እስከ ዕለተ ምጽአት ሲፈጸም የሚኖር ነው፡፡
ለሙታን ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግ፣ መሥዋዕት እንዲቀርብላቸው በቤተ ክርስቲያንና በመካነ መቃብራቸው እንዲጸለይላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት በቀኖና ሐዋርያት አዝዘዋል፡፡ በክርስቶስ አምነው ስለሞቱ ወንድሞቻችሁ ክርስቲያኖችና ሰማዕታት በቤተ ክርስቲያን ያለሐኬት ተሰብሰቡ፡፡ በቤተ ክርስቲያን መሥዋዕት ሠውላቸው፤ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወደ መቃብር ስትወስዱአቸውም መዝሙረ ዳዊት ድገሙላቸው፡፡ ዲድስቅልያ አንቀጽ 33 ገጽ 481
ነቢዩ ዳዊትም የጻድቅ ሞቱ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነው፡፡ ነፍሴ ሆይ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሽ፣ እግዚአብሔር ረድቶሻልና፣ ነፍሴን ከሞት አድኖአታልና፡፡ በማለት ሙታን በጸሎት፣ በምስጋና፣ በመሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር እንዲሸኙ በመዝሙሩ ተናግሯል፡፡ /መዝ. 115፤114-7/
የቤተ ክርስቲያን የሕግና የሥርዓት መጽሐፍ ፍትሐ ነገሥትም በፍትሕ መንፈሳዊ በዲድስቅልያ የተጠቀሰውን ያጸናል፡፡ /አንቀጽ 22/ ስለ ሙታን የሚጸለየው መጽሐፈ ግንዘትም ካህናት ለሞቱ ሰዎች ሊጸልዩላቸው፣ በመሥዋዕትና በቁርባን ሊያስቧቸው ይገባል ይላል፡፡ ካህናት ጸሎተ ፍትሐት በሚያደርጉላቸው መሥዋዕት እና ቁርባን ስለ እነርሱ በሚያቀርቡላቸው ጊዜ መላእክት ነፍሳቸውን ለመቀበል ይወርዳሉ፡፡ ኃጢአተኞች ከሆኑ ስለ ሥርየተ ኃጢአት ይለምኑላቸዋል፤ ይማልዱላቸዋል፡፡ ንጹሐንም ከሆኑ ደስ ይላቸዋል፡፡ ሰውን ለወደደው ለእግዚአብሔር በሰማያት ክብር ምስጋና ይገባል፣ በምድርም ሰላም፡፡ እያሉ እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ ይህም የመላእክት ምስጋናና ደስታ ስለ ሰው ልጅ ድኅነት ነው ተብሎ ተጽፎአል፡፡
የደጋግ ሰዎችን ነፍሳት ቅዱሳን መላእክት እንደሚቀበሏቸው በቅዱስ ወንጌል ተጽፎአል፡፡ አልዓዛርም ሞተ፤ መላእክትም ወደ አብርሃም ዕቅፍ ወሰዱት፡፡ /ሉቃ. 16፤22/
ምንጭ፡-ሃይማኖት የለየንን መቃብር አንድ አያደርገንም፤ ገጽ 20